በሥራ አካባቢ ደኅንነትና ጤንነት ላይ ያተኮረ የሁለት ቀናት ሥልጠና ከኮርፖሬሽኑ ዋና መሥሪያ ቤትና ከንግድ ሥራ ዘርፎች ለተውጣጡና በተለያዩ መደቦች ላይ ለሚሠሩ የሥራ መሪዎችና ሠራተኞች ከግንቦት 9-12/2014 ዓ/ም በሁለት ዙር በዋናው መሥሪያ ቤት የሥልጠና አዳራሽ እየተሰጠ ይገኛል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በስፋት እያካሄደ የሚገኘው የአቅም ግንባታ እንቅስቃሴ አንድ አካል የሆነውና ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር እየተሰጠ የሚገኘው ይህ ሥልጠና በሥራ አካባቢ ደኅንነትና ጤንነት ዙሪያ የሠራተኛውን ዕውቀትና ክህሎት በማጎልበት ኮርፖሬሽኑና ሠራተኛውን ለአደጋ ሊያጋልጡ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሞ በመተንበይና ተመጣጣኝ የመፍትሔ አማራጮችን በማስቀመጥ ተቋሙ ዓላማዎቹንና ግቦቹን እንዲያሳካ የራሱን አስተዋጽዖ እንደሚያበረክት ተገልጿል፡፡
ሥልጠናው በዋነኝነት በመሠረታዊ የደህንነትና ጤንነት መሠረታዊ ሃሳቦች፣ በሥራ ቦታ ስጋት ግምገማና መቆጣጠሪያ ዘዴዎች፣ በሥራ አካባቢ የደኅንነት ጠንቆችና የመከላከያና መቆጣጠሪያ መንግዶች ላይ ያተኮረ ሲሆን፤ ተሣታፊዎች በሥልጠናው ያገኙትን ክህሎትና ግንዛቤ ወደ ተግባር በመቀየር ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል፣ በሥርዓት የሚመራና በቅንጅት የሚፈጸም የልማት እንቅስቃሴ እንዲኖር ለማድረግ የራሱ አስተዋጽዖ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡ |