የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ከኩሽላደር ኮንስትራክሽን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት ጋር የህንጻ ሙሉ እድሳት (ሪኖቬሽን) የውል ስምምነት ግንቦት 15 ቀን 2016 ዓ/ም አደረገ፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አቻ ደምሴ እና የህንጻ እድሳት የሚያከናውነው የኩሽላደር ኮንስትራክሽን ጄነራል ማናጀር አቶ አዲሱ ሞሲሳ የውል ስምምነት ፊርማውን ያከናወኑ ሲሆን ስምምነቱ የዋና መ/ቤት ብሎክ ሁለት ህንጻን ሙሉ እድሳት ለማድረግ የተካሄደ ነው፡፡

በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ወቅት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አቻ ደምሴ የህንጻ እድሳቱ ዋና ምክንያት መጪውን ጊዜ የሚመጥን የቢሮ አደረጃጀት እንዲኖርና ለሥራ ምቹ የሆነን ከባቢ ለመፍጠር መሆኑን ጠቁመው፤ የህንጻ እድሳት የሚያከናውነው ድርጅት በጥራትና በጊዜ ስራውን እንዲያከናውን አሳስበዋል፡፡

የኩሽላደር ኮንስትራክሽን ጄነራል ማናጀር አቶ አዲሱ ሞሲሳ በበኩላቸው ድርጅታቸው ፕሮጀክቶችን በወቅቱ ፈጽሞ የማስረከብ ልምድ እንዳለው ገልጸው፤ የስራ ብቃታቸውን በማሳየት ሌሎች ፕሮጀክቶችንም ከኮርፖሬሽኑ ጋር መስራት እንደሚፈልጉ ተናግረዋል፡፡

የህንጻ እድሳቱ በሶስት ምእራፍ የሚከናወን ሲሆን የመጀመሪያው ምእራፍ ከ20 ቀናት በኋላ እንደሚጀመር ይጠበቃል፡፡

9-Months-Performance.jpg
ኮርፖሬሽኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተለያዩ ገበያ የማረጋጋት ተግባራትን አከናውኗል፡፡ ከእነዚህም ዋና ዋናዎቹ፡-
ለአምራቹ ምርት ገበያ መፍጠር 
ለአርሶ አደሩ ምርት የገበያ ዕድል በመፍጠር ረገድ፡- የአርሶ አደሩን ምርታማነት በቀጣይነት ለመደገፍ ኮርፖሬሽኑ 1,088,387 ኩንታል እህልና 1,691 ኩንታል ቡና እንዲሁም 51,191 ኩንታል ፍራፍሬ እና አትክልት ከምርት አቅራቢዎች ገዝቷል፡፡
ለፋብሪካ ምርቶች የገበያ እድል በመፍጠር ረገድ፡- ኮርፖሬሽኑ ብር 1,332,673,625 ዋጋ ያለው 228,828 ኩንታል ምርት (የፍጆታ ሸቀጥ፣ የስንዴ ዱቄትና ሲሚንቶ) ከሃገር ውስጥ ፋብሪካዎች በመግዛት የገበያ ዕድል ፈጥሯል፡፡
የአቅርቦት እጥረትንና የዋጋ ንረትን ለመከላከል የተደረገ ጥረት
የምርት አቅርቦትን በመጨመር የዋጋ ንረትን ለመቀነስና ገበያውን ለማረጋጋት እንዲቻል ኮርፖሬሽኑ ለመንግሥት ሠራተኞች፣ ለማረሚያ ቤቶችና ሌሎች ሸማች የህብረተሰብ ክፍሎች ብር 136,853,380 ዋጋ ያለው 18,725 ኩንታል ጤፍ፣ ብር 303,071,921 ዋጋ ያለው 47,402 ኩንታል አትክልትና ፍራፍሬ፣ ብር 1,196,046,623 ዋጋ ያለው 11,003,000 ሊትር የምግብ ዘይት፣ ብር 264,509,236 ዋጋ ያለው 38,498 ኩንታል ስኳር፣ ብር 735,275,582 ዋጋ ያለው 86,000 ኩንታል የስንዴ ዱቄት፣ ብር 667,267,407 ዋጋ ያለው 86,400 ኩንታል ልዩ ልዩ የፍጆታ ሸቀጦች አሰራጭቷል፡፡
በሌላ በኩል ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ቀለብ የሚሆን 49,133 ስንዴ እና 86,000 የስንዴ ዱቄት በማቅረብ ሀገራዊ ተልዕኮን ለመወጣት ጥረት ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም የምርት አቅርቦት እጥረትን ለመሸፈን በተለይም ለአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን እና ለዓለም ምግብ ድርጅት /WFP/ ብር 242,489,176 ዋጋ ያለው 69,054 ኩንታል በቆሎ ተሠራጭቷል፡፡ በተመሳሳይ በግንባታው ዘርፍ እየገጠመ ያለውን ከፍተኛ የሆነ የሲሚንቶ አቅርቦት እጥረትና ዋጋ መናርን ለመከላከል ከፋብሪካዎች ብር 97,513,425 ዋጋ ያለው 97,179 ኩንታል ሲሚንቶ በቀጥታ በመረከብ ለተጠቃሚው በተመጣጣኝ ዋጋ ማሰራጨት ተችሏል፡፡
የኮርፖሬሽኑ የሸማች ገበያ ማረጋጋት አስተዋፅኦ በገንዘብ ሲመዘን፡-
በዘጠኝ ወራት ውስጥ በነበሩት ልዩ ልዩ ሀይማኖታዊ በዓላት ምክንያት ሸማቹ ማህበረሰብ በርካታ የፍጆታና ሌሎች ሸቀጦች ግዥ በስፋት የሚያከናዉንበት መሆኑን በመገንዘብና አስቀድሞ ዝግጅት በማድረግ ኮርፖሬሽኑ ገበያ ለማረጋጋት የራሱን አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ በአጠቃላይ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ልዩ ልዩ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ ያቀረበ ሲሆን የኮርፖሬሽኑ መሸጫ ዋጋ በወቅቱ ከነበረው የገበያ ዋጋ ጋር ሲነፃፀር በጠቅላላ የብር 1,820,799,021 ቅናሽ ተደርጓል፡፡

በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ልማት ድርጅት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት የኢትዮጵያ ንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽንን ያለፉት ስድስት ወራት የስራ አፈጻጸም ጥር 8/ 2016 ዓ.ም በአካል ተገኝተው ግምገማ አካሄዱ፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የተከበሩ ፕሮፌሰር መሐመድ አብዱ የኢትዮጵያ ንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን የፍጆታ ምርቶች ላይ የሚስተዋለውን የዋጋ ንረት ለማረጋጋት አበረታች ስራዎችን ስለመሰራቱ ጠቁመው፤ ነገር ግን የአፈጻጸም ጉድለት ያለባቸውን በስፋት አቅዶ መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል::

የኢትዮጰያ ንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አቻ ደምሴ የቋሚ ኮሚቴው አባላትን በአከል ተገኝተው ግምገማ በማድረጋቸው አመስግነው፤ በኮሚቴው እየተደረገ ያለው ድጋፍ ጥሩ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ አክለውም በተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች የሚስተዋለው የፀጥታ ችግር እና ህገ ወጥ የንግድ ስርአት ለተቋሙ ተግዳሮት እንደሆነ ተናግረው በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚገኙት የተቋሙ ይዞታዎች ከህግ አግባብ ውጪ እየተወረሰ በመሆኑ የተቋሙ ህልውና አደጋ ላይ መሆኑንም ዋና ስራ አስፈፃሚው አስረድተዋል።

ኮርፖሬሽኑ ባለፉት 6 ወራት ካቀረባቸው የሽያጭ ምርቶች ከመደበኛው የግብይት ዋጋ በጠቅላላው 1.3 ቢሊዮን ብር ተቀናሽ በማድረግ በገበያ ማረጋጋቱ ስራ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከቱን በቀረበው ሪፖርት ተመላክቷል።

የቋሚ ኮሚቴው አባላት የኮርፖሬሽኑን ያለፉት ስድስት ወራት እቅድ አፈጻጸምን ከመገምገም ባለፈ ከኮርፖሬሽኑ መሰረታዊ ሰራተኛ ማህበር አባላት ጋር ውይይት አድርገዋል፡፡ በተጨማሪም ቃሊቲ የሚገኙትን የፍጆታ እቃዎች ንግድ ስራ ዘርፍ መደብርና የቡና ማእከል፣ ሳሪስ የሚገኘውን የእህል ማከማቻና ማደራጃ ማእከል እንዲሁም የኮርፖሬት ሎጀስቲክስና ቴክኒክ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት የስራ እንቅስቃሴ ከጎበኙ በኋላ  ግብረ መልስ ሰጥተዋል::

በማጠቃለያው የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የተከበሩ ፕሮፌሰር መሐመድ አብዱ ከኮርፖሬሽኑ ተልእኮ ጀምሮ ግልጽነት ስለመፈጠሩና ተቋሙን በደንብ እንዲያውቁት መደረጉን ገልጸው፣ ኮርፖሬሽኑ ያሉበትን ብዙ ተግዳሮቶች እንዲፈታ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡ አክለውም ሰራተኛውና ማኔጅመንቱ ተደጋግፎ መስራቱ እንዲሁም ዋጋ ለማረጋጋት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል::

 

 photo_1_2024-01-18_09-55-17.jpg  photo_2_2024-01-18_09-55-17.jpg

photo_3_2024-01-18_09-55-17.jpg  photo_2024-01-18_09-58-16_2.jpg

photo_4_2024-01-18_09-55-17.jpg

 

Kaizen01.jpg
የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ከካይዘን ልህቀት ማዕከል ጋር የካይዘን ፕሮጀክት ትግበራ የመግባቢያ ስምምነት ፊርማ ሥነ-ሥርዓት መጋቢት 02/ 2016 ዓ.ም አካሄደ፡፡ የመግባቢያ ስምምነት ሰነዱን አቶ አቻ ደምሴ፣ የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ እና አቶ ለቤዛ አለሙ የካይዘን ልህቀት ማዕከል የአገልግሎት ተቋማት ጥራትና ምርታማነት ማሻሻያ ዘርፍ ም/ ሥራ አስኪያጅ ተፈራርመዋል፡፡


የመግባቢያ ስምምነቱ ከመጋቢት 5/ 2016 ዓ.ም እስከ ነሀሴ 30/ 2016 ዓ.ም ለሚተገበረው ችግር ተኮር ፕሮጀክት መር የአመራር ፍልስፍና የተመረጡ ቁልፍ የኮርፖሬሽኑ ችግሮችን በቀጣይነት ለመፍታት እና የተሻለ ውጤት ለማምጣት እንዲሁም ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑ ተመልክቷል፡፡


በመግባቢያ ስምምነቱ ላይ አቶ አቻ ደምሴ ኮርፖሬሽኑ የጀመራቸውን የለውጥ ሥራዎች ለማስቀጠልና ውጤታማ ለመሆን ካይዘን ዓይነተኛ መሳሪያ መሆኑን ጠቅሰው ከካይዘን ልህቀት ማዕከል የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባው ገልጸዋል፡፡
አቶ ለቤዛ አለሙ በበኩላቸው የተሻሉ የካይዘን አማካሪዎችን በመመደብና የጋራ እቅድ በማውጣት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ጠቁመው የኮርፖሬሽኑ አመራር ለካይዘን ትግበራ ለሚያደርገው ጥረት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በሀገራችን ከህዳር 16 እስከ ታህሣሥ 1 ቀን 2016 ዓ.ም የተከበሩት ዓለም አቀፍ የኤድስ ቀን እና የፀረ ጾታዊ ጥቃት (የነጭ ሪባን) ቀንን በተለያዩ ስፖርታዊ ውድድሮች ታህሳስ 20/ 2016 ዓ.ም አከበረ፡፡

 

በመርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልእክት ያስተላለፉት የኮርፖሬት የሕግ፣ ማህበራዊ ጉዳዮችና አሠራር ማሻሻያ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ተወካይ አቶ ይርጋሸዋ ተሾመ አለም አቀፍ የኤድስ ቀን እና የፀረ ጾታዊ ጥቃት (የነጭ ሪቫን) ቀን በየዓመቱ የምናከብረው ለበአልነት ብቻ ሳይሆን ግንዛቤ ለመፍጠር በማሰብ ነው በማለት ሴቶችን ከማንኛውም ጥቃት መከላከል እንደሚገባ እንዲሁም ችላ እየተባለ የመጣው የኤችአይቪ ቫይረስ (ኤድስ) ልዩ ትኩረት እንደሚያስፈልገው በመጥቀስ የኮርፖሬሽኑ ሰራተኞች ጤናቸውን መጠበቅ እንዳለባቸው በአጽንኦት ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም በኮርፖሬሽኑ ሲካሄድ የቆየው ስፖርታዊ ውድድር ለአንድ ዓላማና ለአንድ ግብ በጋራ የመስራት የኮርፖሬት መንፈስን ለመፍጠር እንደተዘጋጀ ጠቁመው አንድ ጠንካራ የእግር ኳስ ቡድን በመመስረት በቀጣይ ከሌሎች ተቋማት ጋር ውድድር እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡

 

በኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ስር በሚገኙት ንግድ ሥራ ዘርፎችና ዋናው መ/ቤት መካከል ለወራት ሲደረግ የነበረው የእግር ኳስ ውድድር ሲጠናቀቅ የፍጆታ እቃዎች ን/ሥ/ ዘርፍ (አለ በጅምላ) እግር ኳስ ቡድን የዋንጫ ባለቤት ሆኗል፡፡ በፍጻሜ ጨዋታ የፍጆታ እቃዎች ን/ሥ/ ዘርፍ የእህልና ቡና ን/ሥ/ ዘርፍን 4 ለ 1 በሆነ ውጤት አሸንፏል፡፡ ዋንጫውንም ከኮርፖሬት የሕግ፣ ማህበራዊ ጉዳዮችና አሠራር ማሻሻያ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ተወካይ አቶ ይርጋሸዋ ተሾመ እጅ በመቀበል ከደጋፊዎቻቸው ጋር በልዩ ህብረ ዝማሬ በመታገዝ ደስታቸውን ገልጸዋል፡፡ በውድድሩ ሁለተኛ በመውጣት ጥሩ ተፎፎካሪ ለነበረው የእህልና ቡናን/ሥ/ ዘርፍ የእግር ኳስ ቡድን የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል፡፡

 

ከእግር ኳስ ውድድሩ ጎን ለጎን በሴት ሰራተኞች መካከል የሩጫ ውድድር የተካሄደ ሲሆን የማታወርቅ ንጉሴ ከዋና መ/ቤት በአንደኝነት ውድድሩን ያጠናቀቀች ሲሆን ከአንድ እስከ ሶስት ለወጡ ተወዳዳሪዎችና ለአንድ ልዩ ተወዳዳሪ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡

 

01.jpg 02.jpg

 

03.jpg 04.jpg

 

05.jpg