ከግንቦት 1-5/2011 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተካሔደው 12ኛው አዲስ ቻምበር የእርሻና ምግብ አለም አቀፍ ንግድ ትርኢት ከተለያዩ ዘርፎች ልዩልዩ ምርቶችን በማስተዋወቅ ለተከታታይ 5 ቀናት በተካሔደው ንግድ ትርኢት ላይ የኢትጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ተሳትፏል፡፡

ይህም የኮርፖሬሽኑ ዘርፎች ለሚያቀርቡት ምርትና አገልግሎት ከደንበኞች እና ከአቅራቢዎች ጋር ለመገናኘት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡የውጭና የአገር ዉስጥ ደንበኞችን አመለካከት በማሻሻል ረገድም ንግድ ትርኢቱ ሚናው የጎላ መሆኑ ታምኖበታል፡ ከሁሉም በላይ ግን ኮርፖሬሽኑ በህዝብ ዘንድ እውቅና እንዲፈጠርለት ከማድረግ አኳያ ንግድ ትርኢቱ ተኪ የሌለው ሚና ይጫወታል፡፡

በንግድ ትርኢቱ ከእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ፣ ከፍጆታ እቃዎች ንግድ ሥራ ዘርፍ እና ከአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ሥራ ዘርፍ የተለያዩ ምርቶችንና አገልግሎቶችን ለህዝብ የማስተዋወቅ ሥራ ተሰርቷል፡፡

በዚሁ   መሠረት ከተለያዩ የውጭ አቅራቢ ድርጅቶች ጋር ቀጣይ ግንኙነቶችን ማድረግ የሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ውይይት ተደርጓል፡፡ እነዚህ አቅራቢ ድርጅቶችም ኢትዮ-አግሮ ሴፍቲ ኃ/የተ/የግ/ማ የሻይ ምርት ማዘጋጃና ማቀነባበሪያ ፋብሪካ፣ ሊዩስ የምግብ ዘይትና አኩሪ አተር ምርቶች፣ ጭላሎ ምግብ ኮምፕሌክስ ሲሆኑ በቀጣይ አብሮ ለመሥራት የሚያስችል ቅድመ ትውውቅ ሥራ ተሠርቷል፡፡

የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን የ2011 ዓ/ም በጀት ዓመት የ9 ወራት እቅድ አፈጻጸም የኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ የቡድን መሪዎችና ከፍተኛ ባለሙያዎች በተገኙበት ተካሂዷል፡፡ በግምገማው የኮርፖሬሽኑ የእህልና ቡና፣ የፍጆታ ዕቃዎች፣ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የግዥና ማማከር አገልግሎት የንግድ ሥራ ዘርፎች ዕቅድ ክንውናቸውን ቀርቦ ውይይት ተደርጓል፡፡

በእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ በ2011 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ከተለያዩ የሃገር ውስጥ የግዥ ምንጮች 937,034 ኩንታል የብዕር እና የአገዳ እህል፣ ጥራጥሬና ቡና ለመግዛት ታቅዶ 785,481 ኩንታል ግዥ የተከናወነ ሲሆን አፈጻጸሙም 84% ነው፡፡ ሌሎች እህሎች ከመግዣ ዋጋ ንረት ጋር በተያያዘ ግዥ አልተፈጸመም፡፡ ኮርፖሬሽኑ በእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ በኩል ገበያን ለማረጋጋት ተግባር 1.151 ሚሊዮን ኩንታል ከሀገር ውስጥ ገበያ የስንዴ ግዢ ለማከናወን በ2011 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ዕቅድ የተያዘ ቢሆንም በዋጋ መናር ምክንያት በመንግስት እንዳይገዛ በመወሰኑ ግዥ እንዳልተከናወነ በአፈጻጸም ግምገማ ተመላክቷል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በሃገር ውስጥና በኤክስፖርት ሽያጭ በ2011 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ የገበያ ማረጋጋት ሥራን ጨምሮ በሀገር ውስጥና በውጭ ገበያ 5.95 ሚልዮን ኩንታል እህልና ቡና ለመሸጥ አቅዶ 4.25ሚልዮን ኩንታል እህልና ቡና በመሸጥ የዕቅዱን 71 በመቶ መከናወኑ በሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል፡፡ 

በዘጠኝ ወራቱ በወጪ ንግድ 70,500 ኩንታል የታጠበ እና ያልታጠበ ቡና ለመሸጥ አቅዶ 29,760 ኩንታል ቡና ለተለያዩ ሀገሮችና ደንበኞች በመሸጥ የዕቅዱ 42 በመቶ የተከናወነ ሲሆን በዘጠኝ ወራት ውስጥ 8,458,602.59 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ከቡና ኤክስፖርት ገቢ መገኘቱ ተገልጿል፡፡ ሆኖም ግን ከ2010 በጀት አመት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር የ24% ቅናሽ አሳይቷል፡፡

በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ሥራ ዘርፍ 231,071 ኩንታል ፍራፍሬ፣ አትክልት፣ የአትክልት ዘር፣ የፋብሪካ ምርት፣ ስኳር፣ የሃገር ውስጥ ዘይት፣ ፓልም ዘይትና ሌሎች ለመግዛት ታቅዶ 155,323 ኩንታል (የዕቅዱ 67%) መከናወኑ ተገልጿል፡፡ የግዢ አፈጻጸሙ ከ2010 በጀት አመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ28% ቅናሽ ያሳየ ሲን ለዚህም በምክንየትነት የተቀመጡት ጉዳዮች መካከል ዋና የፍራፍሬ አቅራቢ ከሆነው ከላይኛው አዋሽ አግሮ ኢንዱስትሪ የሚነሳው የብርቱካን ምርት መቀነስና በበጀት ዓመቱ ከአምስት ያላነሱ ነጋዴዎች ወደ ግብይቱ በመግባት ምርቱን ማንሳት በመጀመራቸው የአቅርቦቱ ማነስ መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡ ዘርፉ በበጀት ዓመቱ በሃገር ውስጥ ሽያጭ 227,057 ኩንታል ተመሳሳይ ምርቶችን ለመሸጥ ታቅዶ 152,692 የተከናወነ ሲሆን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር በመጠን 23% ቅናሽ አሳይቷል፡፡ በአንጻሩ በውጭ ሀገር ገበያ 9,173 ኩንታል ፍራፍሬ ለመሸጥ ታቅዶ የ4,575 ኩንታል ሽያጭ ማከናወን መቻሉ ተገልጿል፡፡ 

በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች ያሉበት የሥራ ደረጃ በተመለከተ የአትክልት ምርቶች በኮንትራት ለማስመረት ከጂቱ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ጋር የአትክልት ምርቶችን በኮንትራት ለማስመረት ውል መፈረሙና ሲሆን ከሰኔ ወር 2011 ዓ/ም ጀምሮ ለገበያ የማቅረብ ሥራ ይጀመራል ተብሎ እንደሚጠበቅ በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡ 

በሌላ በኩል የፍጆታ ዕቃዎች ንግድ ሥራ ዘርፍ በበጀት ዓመቱ 637,336 ኩንታል የተለያዩ የፍጆታ ዕቃወችን ለመግዛት አቅዶ 358,701 ኩንታል ማከናወኑና የግዥ አፈጻጸሙ ከ2010 በጀት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር የ29% በመቶ ቅናሽ ማሳየቱ ተጠቅሷል፡፡

የግዥ ሥራዎችን እና አቅርቦት በተመለከተ በዘጠኝ ወራቱ አዳዲስ 46 በምርትና በአይነት የተለያዩ ምርቶች ከሀገር ውስጥ ተገዝተው መቅረባቸው የተገለጸ ሲሆን በአዲስ ከቀረቡት ውስጥ 26 ዓይነት ምርቶች ቀድመው ይቀርቡ የነበሩ ነገር ተቋርጠው የነበሩና በአዲስ ውልና ድርድር የቀረቡ መሆናቸው ተመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል 14 አዳዲስ አምራቾችን ወደ ድርጅቱ ማምጣት መቻሉ የተገለጸ ሲሆን በአጠቃላይ 637,336 ኩንታል ምርት ለመሸጥ ታቅዶ 448,632 መሸጡ ተገልጿል፡፡

በግዥና ማማከር አገልግሎት ዘርፍ በዘጠኝ ወራቱ የ580 ሚሊዮን ብር የአገልግሎት ግዥ የተከናወነ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ በገቢ ይመዘገባል ተብሎ ከታቀደው ብር 10.59 ሚሊዮን ውስጥ የተከናወነው ብር 8.37 ሚሊዮን መሆኑ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል በሪፖርት ወራቱ ከምክርና ሥልጠና ገቢ ለማግኘት ታቅዶ ከነበረው ብር 1.3 ሚሊዮን ውስጥ ለተለያዩ 306 መንግሥታዊና መንግሥታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች ለተውጣጡ ሠልጣኞች የግዥ ሥልጠና በመስጠት ብር 1.24 ሚሊዮን ገቢ መገኘቱ ተገልጿል፡፡ በአጠቃላይ 12,377,636.32 ብር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ 9,693,563.23 መከናወኑ ተመልክቷል፡፡

የኮርፖሬሽኑ የዘጠኝ ወራት አፈጻጸም ግምገማ ተሣታፊዎች በቡድን ባካሄዷቸው የቡድን ውይይቶችና የተገመገሙ ሲሆን  የታዩ ችግሮችና የመፍትሔ ሃሳቦች በስፋት ቀርበዋል፡፡ ከተነሱ አበይት ችግሮች መካከል የውጭ አገር ሽያጭ መቀዛቀዝ፣ በአንዳንድ የግብይት ሰብሎች (ለምሣሌ ኑግ፣ በቆሎ፣ ሽምብራ) የሀገር ውስጥ የመግዣ ዋጋ ከውጭ አገር መሸጫ ዋጋ መብለጥና ከፍተኛ የሆነ የምርት ክምችት መኖር፣ የመግዣና መሸጫ ዋጋ ውሳኔ የተማከለ መሆን እና ፈጣን ምላሽ የሚሰጥበት አካሄድ አለመኖሩ፤ የገበያ ማፈላለግ ሥራ በአንጻራዊነት ደካማ መሆን፤ በኮርፖሬሽኑና በዘርፉ መካከል የሥልጣንና ሀላፊነት ግልጽነት ጉድለት መታየቱ፤ በበሀብት አጠቃቀም እና ንብረት አስተዳደር ላይ ችግር መኖሩ፤ የተሟላ የኢንሹራንስ ሽፋን አለማግኘት፤ በግዥና በሽያጭ ደንበኛን የማፈላለግና የማቆየት ችግር ነባር ደንበኞች ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በዘርፉ በመፍትሔ አማራጭነት ከተቀመጡት ሃሳቦች መካከልም እሴት ጨምሮ መሸጥ ላይ የበለጠ ትኩረት ማድረግ፤ የግብይት ሥራዎች በተሻለ ውጤታማ እንዲሆኑ ኮርፖሬሽኑ የገበያ ማፈላለግ ሥራን ከሌሎች አካላት ጋር ተቀናጅቶ መሥራት እንደሚያስፈልገው፤ ሀብትና ንብረቶች ይበልጥ በተደራጀ አኳኋን አግባብነት ያለው ባለቤት ተፈጥሮላቸው እንዲ ተዳደሩ ማድረግ፤ የመጋዘን ጥገና ሥራዎች በወቅቱ ተከናውነው የተሟላ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ 

በተመሣሣይም በአትክልትና ፍራፍሬ የንግድ ሥራ ዘርፍ ክንውን ላይ የተለያዩ ጉዳዮች በተሣታፊዎች የተዳሰሱ ሲሆን፤ የኮንትራት ፋርሚንግ ሥራ ተጠናክሮ አለመቀጠሉ፤  የምርት አቅራቢዎች ቁጥር ውስን መሆኑ፤ የውጭ ምንዛሪ እጥረት፤ በአንዳንድ የሽያጭ ሠራተኞች ላይ የሥነ ምግባር ችግር መታየቱ፤ የምርት ብልሽትን አስቀድሞ የመከላከል ችግር ሙሉ ለሙሉ አለመቀረፉ እንደ ችግር የተነሱ ሲሆን የመሸጫ ሱቆችን ማዘመን፤ የተለያዩ የግንዛቤ ማሳደጊያ ሥራዎችን በማከናወን የአቅራቢዎችን ቁጥር መጨመር፤ አቅም ካላቸው የክልል አምራቾች ጋር የገበያ ትስስር መፍጠር፤ ህገ-ወጥ ንግድን ከሚመለከተው ጋር በመሆን እንዲፈታ ጥረት ማድረግ፤ ከሌሎች ዘርፎች ጋር በተሻለ ተቀናጅቶና ተናብቦ መሥራት በሚሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ መሠራት እንዳለበት ተጠቁሟል፡፡ 

ከፍጆታ ሸቀጦች ንግድ ሥራ ጋር በተያያዘም በተለይም በአለ በጅምላ በብድር የተወሰደው ገንዘብ እንዲመለስ ኮርፖሬሽኑ ከሌሎች ጋር በመተባበር እንዲፈታ ማድረግ እንዲሁም ለፍጆታ አቃዎች በብድር የተሰጠ ገንዘብ እንዲመለስ ማድረግ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እንዲሠራ ሃሳብ ቀርቧል፡፡ 

በተጓዳኝ የሥራ ሂደቶች ክንውን ዙሪያ በተደረጉ የቡድን ውይይቶች ከተነሱ አንኳር ጉዳዮች መካከል ከጅንአድ የተዛወረ 8000 ካ/ሜ መካዝን ወደ ሥራ እንዲገባ ማድረግ፤ የምርት ሥርጭት /በተለይም ወደ መዳረሻ የሚሄዱ ሸቀጦች/ በተሻለ ጥራት እዲከናወን ማድረግ፤ የሂሳብ ምርመራዎች በወቅቱ እንዲካሄዱ ማድረግ፤ የውጤት ተኮር ሥልጠና በተለይ በሥራ አመራሩ ውስጥ ሊያሰርጽ በሚያስችልበት አኳኋን እንዲካሄድ ማድረግ፤ የለውጥ መሳሪያዎች በአውቶሜሽን እንዲደገፉ ማድረግ፤ የኮርፖሬት አስተሳስብን የመፍጠር ሥራዎች ደካማ በመሆናቸው በቀጣይ በተጠናከረ መልኩ ማከናወን፤ የሕዝብ ግንኙነት ሥራዎችን በተሻለ ጥራትና ወቅታዊነት እንዲከናወኑ ማድረግ፤ ለህግ ከቀረቡ ጉዳዮች መካከል 60 በመቶ በማሸነፍ ቀሪው 40 በመቶ ደግሞ በሽነፈት የተጠናቀቁ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ የሽንፈቶቹ መሠረታዊ ምክንያቶች ተለይተው ተገቢው የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ፤ በክርክር ላይ በሽንፈት ምክንያት የሚመጣውን ኪሳራ ለማስቀረት ቅድመ መከላል ላይ ማተኮር፣ የማማከር እንዲሁም ጉዳዮችን በድርድር የመፍታት አቅምን ማዳበር በሚሉት ላይ ትኩረት ተደርጎ መሠራት እንዳለበት ተጠቅሷል፡፡  በመጨረሻም በተነሱ ጉዳዮች ላይ በአመራሩ ሰብሳቢነት አጠቃላይ ውይይት ተደርጎ የግምገማ መድረኩ ተጠናቋል፡፡

የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን በጥሬ ገንዘብና በዓይነት በድምሩ አንድ ሚሊዮን ብር የሚገመት ድጋፍ ለመቄዶኒያ አረጋውያንና የአእምሮ ህሙማን ማዕከል አደረገ፡፡ የኮርፖሬሽኑ አመራርና ሠራተኞች የገናን በዓል ምክንያት በማድረግ ታህሳስ 24 ቀን 2011 ዓ/ም አዲስ አበባ አያት የሚገኘው ማዕከል በመገኘት አረጋውያንና የአእምሮ ህሙማንን ጎብኝተዋል፡፡ የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ለመቄዶኒያ አረጋውያንና የአእምሮ ህሙማን ማዕከል ያደረገው ድጋፍ በጥሬ ገንዘብ ብር 355,873 ሲሆን ቀሪው በዓይነት በድምሩ አንድ ሚሊዮን ብር የሚገመት ነው፡፡ ኮርፖሬሽኑ በዓይነት ለማዕከሉ ድጋፍ ያደረጋቸው ምርቶች 100 ኩንታል ነጭ ጤፍ፣ 20 ኩንታል ሽንብራ፣ 40 ኩንታል ስኳር፣ አንድ ካርቶን (368 ፍሬ) ሻይ ቅጠል፣ 7.5 ኩንታል ማካሮኒ፣ 200 ሊትር ዘይት፣ 236 ሊትር ላርጎ ፈሳሽ ሳሙና፣ 18 ባለሁለት ሊትር ፈሳሽ ሳሙና፣ 100 ፍሬ አጃክስ ሳሙና፣ 20 ኩንታል ሙዝ፣ 10 ኩንታል ብርቱካን፣ 240 ጣሳ ማርማላት፣ 995 ጣሳ ቲማቲም ድልህ እና ግምታቸው አስር ሺህ ብር የሆነ ልባሽ አልባሳት ናቸው፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መንግሥቱ ከበደ እና የሠራተኛ ማህበር ተወካዮች ድጋፉን ለማዕከሉ መስራች ክቡር ዶክተር ቢኒያም በለጠ ማዕከሉን በጎበኙበት ወቅት አስረክበዋል፡፡ በቀጣይ ማዕከሉን በዘላቂነት ለመደገፍ የኮርፖሬሽኑ አመራርና ሠራተኞች ዝግጁ መሆናቸውን ድጋፉ በተደረገበት ወቅት የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መንግሥቱ ከበደ ገልፀዋል፡፡ ኮርፖሬሽኑ የህብረተሰቡን የፍጆታ ዕቃዎችና የምግብ ምርቶች ፍላጎት ለማሟላትና የገበያ ዋጋን ለማረጋጋት የተቋቋመ እንደመሆኑ መጠን ለማዕከሉ የሚያስፈልጉ የእህል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የፍጆታ ዕቃዎች በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ዘላቂ ድጋፍ ለማድረግ እንደተዘጋጀም ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ የንግድ ሥ ራዎች ኮርፖሬሽን በ2010 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀምና በ2011 በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ ከደንበኞችና ባለድርሻ አካላት ጋር ህዳር 4 ቀን 2011 ዓ/ም በግሎባል ሆቴል ውይይት አካሂዷል፡፡

በኮርፖሬሽኑ የኮርፖሬት አገልግሎት ም/ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ታሪኩ በራሱ የምክክር መድረኩን ሲከፍቱ የኢትዮጵያ የንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን በ2010 በጀት ዓመት በሀገር ውስጥ እና በውጭ ገበያ 7.21 ሚሊዮን ኩንታል እህል፣ ቡና፣ አትክልትና ፍራፍሬ እና የፍጆታ ዕቃዎች ለመሸጥ አቅዶ 7.77 ሚሊዮን ኩንታል ያከናወነ መሆኑን በ2011 በጀት ዓመት 8.72 ሚሊዮን ኩንታል ለመሸጥ ማቀዱን ገልጸዋል፡፡

የደንበኞች አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል በበጀት ዓመቱ አሰራሩን በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮችን የመተግበርና የሰራተኞቹን አቅም የሚያጎለብቱ በካይዘን አመራር ፍልስፍና ጽንሰ ሃሳብ፣ በአለም አቀፍ የፋይናንስ ሪፖርት አዘጋገብ / IFRS /፣ በምርት ጥራትና ክምችት አያያዝ እንዲሁም በውጭ ንግድ ሥርዓት ላይ ያተኮሩ ሥልጠናዎች ለኮርፖሬሽኑ አመራርና ፈጻሚዎች መስጠቱን ም/ዋና ሥራ አስፈፃሚው ተናግረዋል፡፡

ለገበያ ማረጋጊያ በኮርፖሬሽኑ የሚቀርቡ ምርቶችን ጥራት ማረጋገጥ፣ ምርቱ መቼ፣ የት እና በማን እንደተገዛ የሚገልፅ ግልጽ አሠራር ተግባራዊ ማድረግ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችን አቅርቦት ሳይቆራረጥ ለተጠቃሚው ለማቅረብ የኮንትራት ፋርሚንግን አሠራርን ተግባራዊ ማድረግ፣ የፍጆታ ዕቃዎች ተደራሽነትን ለማሳደግም አቅርቦትና ፍላጎትን ማጣጣም የሀገር ውስጥና አለም አቀፍ ግዥዎች የመፈጸም አቅምን ማሳደግ በበጀት ዓመቱ ትኩረት የተሰጣቸው ሥራዎች እንደሆኑ በውይይቱ ወቅት ተገልጿል፡፡

ኮርፖሬሽኑ ደንበኞቹና ባለድርሻ አካላት በሚጠብቁበት ደረጃ አገልግሎቱን ለመስጠት እና ባቀደው ዕቅድ ልክ አፈጻጸሙን ለማሳካት በሀገር ውስጥ በሚፈለገው መጠንና ዋጋ የእህል ምርት ገበያው ላይ አለመገኘት፣ በመንግሥት ድጎማ ለገበያ ማረጋጊያ ከውጭ ሀገር የሚገዛውና በኮርፖሬሽኑ የሚሰራጨው የውጭ ስንዴ ግዥ ጨረታ መስተጓጎል ለገበያ ማረጋጊያ ከውጭ ለሚገዙ የፍጆታ ሸቀጥ ምርቶችም በውጭ ምንዛሪ እጥረት ፍላጎትና አቅርቦቱ አለመመጣጠን፣ ኮርፖሬሽኑ ለውጭ ገበያ የሚቀርባቸው የቡና፣ የቅባት እህልና ጥራጥሬ ዋጋ በዓለም አቀፍ ደረጃ ካለው የገበያ ዋጋ መብለጥና የምርቶቹ ዋጋ መዋዥቅ ዋነኛ ችግሮች መሆናቸው በውይይቱ ወቅት ተብራርቷል፡፡

የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው የአገር ውስጥና የውጭ ስንዴ ግዥ ጥራት ኢንዱስትሪውን ታሳቢ ያደረገ እንዲሆን እንዲሁም እያጋጠመ ላለው የፍጆታ እቃዎች እጥረት ኮርፖሬሽኑ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሄ እንዲፈለግ ጠይቀዋል፡፡ በመድረኩ ላይ እህል አቅራቢ የሆኑ አርሶ አደሮች፣ ህብረት ሥራ ማህበራት፣ ለገበያ ማረጋጊያ ከኮርፖሬሽኑ ስንዴ የሚገዙ የዱቄት ፋብሪካ ባለንብረቶች፣ ከኮርፖሬሽኑ በጋራ የሚሠሩ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት፣ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮዎች እና ማህበራዊ ተቋማት ተሣትፈዋል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በወጪ ንግድ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ያስገኙ ላኪዎች፣ ገንዘብ አስተላላፊዎችና አገልግሎት ሰጪ ደንበኞቹን ታህሳስ 11 ቀን 2011 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል ዕውቅና ሰጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ የንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን በ2010 በጀት ዓመት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ በማስገኘት የፕላቲኒየም ተሸላሚ ሆኗል፡፡ ኮርፖሬሽኑ የቡና፣ ቅባት እህሎች፣ ጥራጥሬና የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችን ወደ ተለያዩ ሀገራት በመላክ 26.776 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር አስገኝቷል፡፡ ኮርፖሬሽኑ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በተመሳሳይ ባስገኘው የውጭ ምንዛሪ መጠን ተሸላሚ መሆኑ ይታወቃል፡፡